Site icon Dinknesh Ethiopia

የኢትዮጵያን ጠላትና አሸባሪ ሃይል በጋራ እንመክት፣ በአሸናፊነትም ለድል እንዘጋጅ

Suleman Abdela

የኢትዮጵያን ጠላትና አሸባሪ ሃይል በጋራ እንመክት፣ በአሸናፊነትም ለድል እንዘጋጅ ሲል በሳኡዲ የሚኖረውና ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ጥቅምና እውነታ የሚከራከረው ወጣቱ ሱሌማን አብደላ ተናገረ፡፡

አሸባሪው ህወሃት ስልጣን ላይ በነበረበት ወቅት የራሱን የሌብነት ኔትወርክ ዘርግቶ ኢትዮጵያን ዘርፏል፣ በርካታ ዜጎችን በማሳደድ ገድሏል፣ በማሰር አሰቃይቷል።

ለአሸባሪው ግፍ የተደራጀ ምላሽ ለመስጠት በጋራ የተነሳው ህዝብ ደግሞ ከ27 ዓመታት በኋላ አስወግዶት ኢትዮጵያን ካልዘረፍኳት ላፍርሳት ብሎ በመነሳት የተለያዩ ጥፋቶችን እያደረሰ ይገኛል።

በአፋርና አማራ ክልሎች ወረራ ፈፅሞ ከትምህርት ቤት እስከ ግለሰብ መኖሪያ ቤት፤ ከጤና ጣቢያና ሆስፒታል እስከ አርሶ አደር አዝመራ የቻለውን ዘርፎ የቀረውን አውድሟል።

ኑሮውን በሳውዲ አረቢያ ያደረገውና ስለ አገሩ ኢትዮጵያ ትክክለኛ ገጽታ በመጻፍ፣ የተሳሳተ አመለካከት የሚያራምዱትን በመሞገት የሚታወቀው ወጣቱ ሱሌማን አብደላ አሸባሪው ህወሃት የተበታተነች አገር ለመፍጠር ዓላማ እንዳለው ይናገራል።

የአሸባሪው ህወሃት ስብስብ ኢትዮጵያን ያለከልካይ መዝረፍ የሚችልበት ጊዜ ስላከተመበት “ልበትናት” ብሎ ከሌሎች ጣላቶች ጋር አብሮ የተነሳ ካሃዲ ሃይል መሆኑን ገልጿል።

በመሆኑም ይህንን አገር አፍራሽ ሃይል በተባበረ ክንድ በማሸነፍ ግብአተ መሬቱን ማፋጠን ጊዜ የማይሰጠው ጉዳይ መሆን አለበት ብሏል።

አሸባሪው ህወሃት ከህፃናት እስከ አዛውንት፤ ከነፍሰጡር እስከ አካል ጉዳተኛ ለጦርነት በማሰለፍ የመውረር፣ የመዝረፍና የማሸበር ስራ እያከናወነ በመሆኑ በተደራጀ ህዝባዊ ምላሽ ማሸነፍ ይገባል ብሏል ሱሌማን።

የተደራጀ ህዝብ ሁሌም አሸናፊ ይሆናል እና የኢትዮጵያን ዋነኛ ጠላትና አሸባሪ ሃይል በጋራ እንመክት፣ በአሸናፊነትም ለድል እንዘጋጅ ሲል ተናግሯል።

በተለይ ወጣቶች ሰራዊቱን በመቀላቀል አሸባሪውን ሃይል ፊት ለፊት መፋለም አለባቸው ያለው ሱሌማን ከቻሉ ደግሞ በደጀንነት፣ ስንቅ በማዘጋጀትና በማቀበል እንዲሁም በማበረታታት አገራዊ ግዴታቸውን ሊወጡ ይገባል ብሏል።

ሁሉም ማህበረሰብ ከሰፈር እስከ ሀገር የጸጥታ ዘብ ለመሆን ይበልጥ በመዘጋጀት የአሸባሪውን ሴራ እና የሃሰት ፕሮፓጋንዳ መመከት አለበት ነው ያለው።

የመረጃ ልውውጡን በማጠናከር ለአሸባሪው ቡድን የገንዘብ እና ሌሎች ድጋፎችን ለማድረግ የሚንቀሳቀሱ ሃይሎችን ማጋለጥም የሁላችንም ሃላፊነት ሊሆን ይገባል ብሏል ሱሌማን።

አሸባሪውን ለመመከት በሚደረገው ትግል ንጹሃን ተጎጅ እንዳይሆኑ እያንዳንዱ እንቅስቃሴ በመረጃና በማስረጃ የተደገፈ እንዲሆንና አጥፊዎችንም ለሚመለከተው የህግ አካል ማስረከብ በአሰራራችን ሊጠናከር ይገባል ብሏል።

“ጠላት በመቶዎች ሲመጣ በሚሊዮኖች ልንፈናቀል አይገባም፤ ይልቁንም ተደራጅተንና ተዘጋጅተን በመመከት ጠላት የገባባቸው አካባቢዎች ሁሉ መቀበሪያው ማድርግ አለብን” ነው ያለው።

በመሆኑም አሸባሪውን ለመቅበር ጉልበት ያለው በጉልበቱ፤ ገንዘብ ያለው በገንዘቡ ለማይቀረው ድል የበኩሉን አስትዋጽኦ እንዲያደርግ ጠይቋል።

በተለያዩ አጋጣሚዎች የወገን ሃይልን እንቅስቃሴ ስንገልጽ ለጠላት መረጃ እያቀበልን መሆኑን በመገንዘብ ምስጢር ጠባቂ እንሁን ሲል መልእክቱን አስተላልፏል።

 

Source: https://www.ena.et/

Exit mobile version