Analysis

ህወሀት በድርድር መሀል ወደ ጦርነት እገባለሁ ለምን ይላል?

ህወሀት በድርድር መሀል የሚፈለገውን እያገኘ ወደ ጦርነት እገባለሁ ለምን ይላል?

አክሊሉ ወንድአፈረው

ነሀሴ 13፣ 2014 ( ኦገስት 19፣2022)

Aklilu Wondaferewወሀት በተደጋጋሚ እንዳደረገው ሁሉ ትላንትም ድርድር የሚባል ነገር እንደማይሰራ ብቻ ሳይሆን የተኩስ ማቆም ስምምነቱም እንደከሸፈና ውጊያ ሊገባ እንደሆነ ገልጿል፡፡ ይህ ብቻ አይደለም ተዋጊዎቹን በተለያየ አቅጣጫ ወደ አማራ፣ አፋር ክልልና ወደ ኤርትራ እንዳሰጠጋና የወጊያ ማበረታቻ ጭፈራ እያካሄደ እንደሆነም እየተነገረ ነው፡፡

የህወሀት አስትራተጂ ድርድር እፈልጋልሁ ሆኖም የሚከተሉትን ቅድመ ሁኔታዎች አሟሉ ይህ ካልሆነ ደግሞ በጉልበት የምፈልገውን አሳካለሁ የሚል ነው፡፡ባጭሩ የጉልበት ማስፈራሪያንና ድርድርን አጣምሮ የያዘ ነው፡፡

እስከ አሁን የሚታየው የመንግስት የድርድር እስትራተጂ ትንሽ ደግሞ በተገፋ ቁጥር እምቢ ያለውን የማድረግ አካሄድ ነው፡፡ ለአብነት ህወሀት እስካሁን በማስፈራራት በቅድመ ሁኔታ ካስቀመጣቸው ውስጥ ከመንግስት አራቱን አግኝቷል፡፡ መንግስት ይህን ሲያሟላ በምትኩ ያገኘው አንድም ነገር የለም፡፡ ምናልባት የተወሰነ የውጭ እርዳታ አግኝቶ ይሆናል፡፡

ያም ሆኖ ግን ህወሀት አሁንም ባገኘው ረክቶ በቅን መንፈስ (good faith ) በጠረጰዛ ዙሪአያ ብቻ ድርድር ለማድረግ ብዙም ፍላጎት እያሳየ አለመሆኑ ብቻ ሳይሆን አሁንም በተጸእኖ ወልቃይትን ሁመራን ወዘተ ቢችል ክድርድር በፊት ለማስለቀቅ ካልቻለም ወደ ጠረጰዛ ሲመጣ ድርድሩን ጥሎ ለመውጣት ግድ እንደሌለው በማሳየት በድርድሩ ላይ የበላይነትን ለማገኘት እየጣረ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡

መንግስት ምን ሲሆን ድርድሩን ጥሎ ለመውጣት እንደተዘጋጀ የሚያሳየው ነገር ሰለሌለ በአጠቃላይ አካሄዱ ለብዙ ተጸእኖ የተጋለጠ ነው፡፡ በቀጣይም የመንግስት ተደራዳሪዎች ይህ ግልጽ ሆኖ እስካልተቀመጠላቸው ድረስ በድርድሩ ጠረጴዛ ዙሪያ ቆራጥነት ያንሳቸዋል ይህም ደካማ ተደራዳሪ ያደርጋቸዋል ፣ በመጨረሻም ያስጠቃቸዋል፡ መጥፎ ውል ላይ እንዲደርሱም ያደርጋቸዋል፡፡

ድርድር አልፈልግም ፣ በድርድር የማገኘውን ሁሉ በጉልበቴ ወይም በሌላ በኩል አገኘዋለሁ የሚለው ማስፈራሪያ በድርድር አለም የተለመደ ታክቲክ ነው፡፡ ይህን የማድረግ ችሎታ እንዲሁም ዝግጅት ያለው ተደራዳሪ በአሸናፊነት እንደሚወጣ የተለያዩ በድርድር ላይ የቀረቡ ጸሁፎች ያሳያሉ ፡ይህ አቀራረብ ከፍተኛ ኪሳራንም (high risk ) ሊያስከትል የሚችል ጉዳይ ነው፡፡ በተለይም ተቃራኒው ተደራዳሪ እስኪ እናያለን የምታደርገውን አድርግ የሚል ከሆነና ሊከተል ለሚችለው ሁሉ በቂ ዝግጅት አድርጎ ከሆነ በርግጥም ከፍተኛ ኪሳራን (high risk ) ሊያስከትል የሚችል አካሄድ ነው፡፡ ተደራዳሪህ ድንጉጥ ሲሆን ብዙም ድጋፍ እንደሌለው ወይም ከድርድር ውጭ ብዙም አማራጭ እንደሌለው ስታውቅ ደግሞ እጅግ አዋጭ አካሄድ ነው፡፡በትክክልም ይሰራል ፡፡

ከዚህ አንጻር ድርድር ካልሆነ በጉልበት እሞክረዋልሁ ይኸ ይኸ ካልተሟላ ወደ ድርድር አልመጣም፣ አደራዳሪዎች ሰላስጨነቁን እንጂ የምንፈልገውን በሌላ መንገድ እገናለሁ የሚለው የህወሀት ንግግር ሁሉ፣ ዝም ብሎ የሚወረወር ሳይሆን በስልት፣ ተጠንቶና ተወስኖ የሚሰነዘር የድርድር እስትራተጂ መሆኑን ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ ጦርነት ከምንገባና ኪሳራ ከማምጣት ወዘተ በሚል ማስፈራሪያ የሚፈለጉትን ለማግኘት የተደራዳሪን ሰነ ልቦና ማሰጨነቂያና መስለቢያ እርምጃ ነው፡፡

በኔ እይታ በቢል ለኔ ስዩም የትላንቱ መግለጫ ውስጥ መንግስት ይህ ፍራቻ እንዳለበት ተንጸባርቋል፡፡እንደ መግለጫው ከሆነ በመንግስት በኩል ልበ ሙሉነት ፣ አልታየም ፣ እስኪ ሞክሩት ይህን ቀልድ ተው የሚል ነገር አልተሰማም ፡፡

የህወህት የሚፈልገውን አራት ነገር አግኝቷል፡፡ አሁን ደግሞ ዋናው ትኩረቱ ወልቃይት ሲሆን ይህን ለማግኘት በድርድር ካልሆነ በጡንቻ አደርገዋለሁ በማለት ጦሩን በአራት አቅጣጫ በማንቀሳቀስ መንግስትንም አደራዳሪዎችንም ሊያስሸብር እየጣረ ነው፡፡

መንግስት ደግሞ ያለውን ሁለንተናዊ ዝግጅት በተለይም በወታደራዊ ዝግጅቱ ጠንካራ መሆኑን አየር ሀይልን ለባለድርሻዎች በማስጎብኘት የ ህወሀትን ዝግጅት ደካማ ነው በማለት ወዘተ ባለፉት ሳምንታት በገደምዳሜ መልእክቱን ሲያስተላልፍ የቆየ ቢሆንም ምን ሲፈጠር ድርድር ሊቀጥል እንደማይችል የሚያሳየው ፍንጭ ግን የለም፡፡

በተጨማሪም አንድም ነገር ከህወሀት ሳያገኝ በሚሊዮን የሚቆጠር ዶላር ተላልፎ እንዲሰጥ መፍቀዱ፣ የባንክ የቴሌ ወዘተ አገልግሎት ያላንዳች ቅድመ ሁኔታ መልቀቁ፣ የተኩስ ማቆም ስምምነት ለማድረግ ዝግጁ ነኝ ማለቱ (ጥድፊያ ማሳየቱ) የርዳታ አቅርቦት ያላንዳች ገደብ እንዲተላለፍ ማድረጉ፣ ሀወሀትን አሁንም ተጨማሪ ግፊት ባደርግ ወጤታማ እሆናለሁ ብሎ እንዲደመድም ያደረገው ይመስላል፡፡ ይህ በተራው ህዝብ (ordinary citizens ) ዘንድ ቀጣዩስ ምን ይሆን የሚል ግርሞትን ማሰከተሉ አይቀርም፡፡

ከሳምንት በፊት መንግስት ከላይ የተጠቀሱትን በድርድር ጠረጰዛው ዙሪያ መታየት አለባቸው ሲል እንደነበር አይረሳም፡፡ ዛሬ ደግሞ ሁሉንም እርግፍ አድርጎ ያለ አንዳች ቅድመ ሁኔታ እቀበላለሁ ብቻ ቶሎ አደራድሩኝ ነው ወይዘሮ ቢል ለኔ ያሉት፡፡ ይህ የተምታታ አካሄድ ሀወሀትን በማያምኑና በሚፈሩ ክፍሎች በተለይም የወልቃይት ሁመራ ቃፍታ፣ ጠለምትና ራያ ጉዳይ ለሚያሳስባቸው በሚሊዮኖች ለሚቆጠሩ ሁሉ አስጨናቂ ቢሆን የሚገርም አይደለም፡፡ይህ የልብ አለመገናነት ደግሞ በመንግስት እና ህዝብ መሀል ያለውን ግንኙነት ይበልጥ ይሸረሽረዋል፡፡ መንግስት ይህን በአስቸኳይ ሊያርም ይገባል፡፡

የህወሀትን ማስፈራሪያና የመንግስትን ምላሽ ተከትሎ ትላንት እና ዛሬ የውጭ መንግስታት በተለይም ምእራባውያኑ መግለጫ በማውጣት በመንግስት ላይ ያነጣጠረ ታላቅ ተጸእኖ ማድረግ ጀምረዋል፡፡ የአለም ጤና ጥበቃው ዶክተር አድሀኖምም እንደተለመደው ያቅሙን ያክል ተጸእኖ ለማሳደር እየሞከረ ነው፡፡

እነዚህ ሁሉ በድርድሩ ዙሪያ ምን ሊያደርጉ እንደሚችሉ መገመት አይከብድም፣ በአሁኑ ሰአት በ ዋሽንግተን በአዲስ አበባና ብራስልስ ባልስልጣናት መሀል የሚካሄደውን የስልክ ልውውጥ ብዛትና ይዘት መገመት ልዩ ችሎታን የሚጠይቅ አይሆንም ፡፡ ሁሉም ደጋግመው ደጋግመው ወልቃይትን እንደሚያነሱ አትጠራጠሩ፡፡ የሚገርመው የአለምን ታላላቆች ሳይቀር እያሯሯጠ የሚገኘው ሁኔታ የሀገራችንን ተቃዋሚ ፖለቲከኞች ሊያንቀሳቅስ አለማቻሉ ነው፡፡ ዘይገርም፡፡

ፈጣሪ ሀዝባችንንና ሀገራችንን ይጠብቅ

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *