ኢዜማ
Press Release

ሕዝብ የአስተዳደር ውሳኔን የመቀበል ግዴታ የሚኖርበት እንደ ዜጋ ሂደቱ ላይ የመሳተፍ እና የማወቅ መብቱ በአግባቡ ሲከበርለት ብቻ ነው!

የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የብሔራዊ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ ለመረዳት እንደቻለው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እና የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት የአስተዳደር ወሰን ለማካለል የሚያስችል ስምምነት ላይ መድረሳቸውን ነው። መሬት ላይ ያሉ ችግሮችን ለመፍታት የአስተዳደር ወሰን ማካለሉ ጠቃሚ መሆኑ ባይካድም ውሳኔዎቹን ማስተግበር የሚቻለው ዜጎችን አሳትፎ የሂደቱ ባለቤት በማድረግ እንጂ በኃይል ለመጫን የሚደረግ ሙከራ ከጥቅሙ ጉዳቱ እንደሚያመዝን ሊታወቅ ይገባል፡፡

ይህ ወሰን ማካለል ምን ዝርዝር ውሳኔዎች እንደያዘ በጥልቀት የሚጣራ ይሆናል። ፓርቲያችን ሀገራዊ ምክክሩ ይፈታቸዋል ብሎ ከሚያስባቸው ጉዳዮች አንዱ ይህን መሰል የአስተዳደር አከላለል ጉዳዮች ሆኖ እያለ እንደ ሀገር ያለንበትን ወቅት ከፍተኛ ችግር ታሳቢ ያላደረጉ እንደ ክላስተር እና የአስተዳደር ወሰን ማካለል ዓይነት ውሳኔዎችን እየሰማን ነው። ጉዳዩን የምናየው “ማን ምን አገኘ? ማንስ ምን አጣ?” በሚል ቁንጽል እሳቤ ሳይሆን ከአግባብነቱ እና ጊዜውን ካለመጠበቁ አንፃር ከፍተኛ ስህተት ሆኖ አግኝተነዋል። በፍጥነት ሊታረም እንደሚገባም ልናሳስብ እንወዳለን፡፡

እንደ ኢዜማ እምነት በአካባቢው እየኖረ ያለው ሕዝብ የመንግሥትን ውሳኔዎች የመቀበል ግዴታ የሚኖርበት እንደ ዜጋ ሂደቱን የማወቅ እና የመሳተፍ መብቱ ሲከበርለት ብቻ መሆኑ ሊታወቅ ይገባል፡፡

ፓርቲያችን አዲስ አበባ ላይ እየተስተዋሉ ያሉ የአስተዳደር መደበላለቅ ችግሮችን በተመለከተ ዝርዝር መረጃዎችን ሰብስቦ በጥናት የሚለይ ቡድን አቋቁሞ ቀደም ብሎ ሥራዎችን እንደጀመረ በሚዲያ መግለጹ ይታወቃል። ጥናቱ ሲጠናቀቅም ውጤቱን ለሕዝብ ይፋ የሚያደርግ ይሆናል፡፡

የኢዜማ ብሔራዊ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ

ነሐሴ 05 ቀን 2014 ዓ.ም.

አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *