Alamata
Current News

ከአላማጣ በታጣቂዎች ተገደው የተወሰዱ አሥር ሺሕ ወጣቶች ያሉበት እንደማይታወቅ ተገለጸ

ቀን: February 5, 2023

  • ያለ ፍርድ የታሰሩ 295 አመራሮችና ወጣቶች እንዲፈቱ ተጠየቀ

በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ወቅት በታጣቂዎች ተገደው የተወሰዱ አሥር ሺሕ ወጣቶች ያሉበት እንደማይታወቅ የአላማጣ ከተማ አስተዳደር አስታወቀ፡፡

የከተማ አስተዳደሩ የፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ሞገስ እያሴ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በጦርነቱ ወቅት በሕወሓት ታጣቂዎች ተይዘው ታስረዋል የተባሉ 295 የመንግሥት አመራሮችና ወጣቶች በአስቸኳይ እንዲፈቱም የከተማው አስተዳደርና የታሳሪ ቤተሰቦች ጥያቄ ማቅረባቸውንም አክለዋል፡፡

እስረኞቹ የሚገኙት በማይጨው ማረሚያ መሆኑን ጠቁመው፣ በአስቸኳይ እንዲፈቱ ለሚመለከታቸው የመከላከያ ሠራዊት አዛዦች በደብዳቤ እንዳሳወቁም ገልጸዋል፡፡

በማይጨው ማረሚያ ቤት ይገኛሉ የተባሉት ታሳሪዎቹ ከአላማጣ፣ ከባላ፣ ከጨርጨር፣ ከኮረምና ከኦፍላ የተወሰዱ ናቸው ተብሏል፡፡

አመራሮችን ጨምሮ 295 ሰዎች በሕወሓት ታጣቂዎች እንደታሰሩ የገለጹት ኃላፊው፣ ከእስር የተፈቱና የታሳሪ ቤተሰቦች የሚመለከተው አካል በአስቸኳይ እንዲያስፈታላቸው ጠይቀዋል፡፡

የሕወሓት ታጣቂዎች በጦርነቱ ወቅት ካሰሯቸው ወጣቶችና አመራሮች መካከል 15 ያህሉ የአላማጣ ከተማ የመንግሥት አመራሮች መሆናቸውንም አቶ ሞገስ አስታውቀዋል፡፡

በከተማዋ ዙሪያ ያለው የፀጥታ ሁኔታ ሰላም መሆኑን ጠቁመው፣ በማይጨው ማረሚያ ቤት በእስር ላይ የሚገኙ ሰዎችን ለማስፈታት በሒደት ላይ ቢሆኑም፣ አሥር ሺሕ ወጣቶች ግን ያሉበት አለመታወቁ አሳሳቢ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

የአማራ ክልል ፍትሕ ቢሮ ሪፖርተር ላቀረበለት ጥያቄ በሰጠው ምላሽ፣ ታሰሩ ስለተባሉት ሰዎች የደረሰው መረጃ ስለሌለ አስተያየት መስጠት እንደማይችል ገልጿል፡፡

እስረኞቹ የሚገኙት በአማራና በትግራይ ክልሎች የወሰን ውዝግብ በሚስተዋልባቸው አካባቢዎች መሆኑን፣ ከእስር የተፈቱ የዓይን እማኞችና የታሳሪ ቤተሰቦች ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

አመራሮቹ የታሰሩት ‹‹የብልፅግና ደጋፊዎች ናችሁ›› ተብለው መሆኑን ከእስራት የተፈቱ ሁለት የዓይን እማኞች ገልጸዋል፡፡ የታሰሩት ከሐምሌ 5 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ እንደሆነ የገለጹት የዓይን እማኞች ከአላማጣ ወደ ኮረም፣ ከኮረም ወደ ማይጨውና ወደ አዲሸሁ እስር ቤት ሲዘዋወሩ እንደነበር አስረድተዋል፡፡

ታሳሪዎቹ በአብዛኛው ዕድሜያቸው ከ25 እስከ 30 ቢሆንም፣ ሦስት ሴቶችና ሁለት የ82 እና 85 የዕድሜ ባለፀጋዎች ታስረው እንደነበርም ገልጸዋል፡፡

በአጂሸሁ ግራውንድ ማረሚያ ቤት የነበሩ 270 ያህል እስረኞች፣ ‹‹በቀን ሦስት ጊዜ የሚገረፉ፣ ለአንድ ወር ቤት ተዘግቶባቸው በጨለማ ውስጥ የኖሩ፣ የውኃና የምግብ አቅርቦት የማያገኙ›› እንደነበሩ ታስረው የተፈቱት ታራሚዎች ለሪፖርተር አስረድተዋል፡፡

በማረሚያ ቤት ከነበሩት መካከል ሁለት ሰዎች በረሃብ ሞተዋል ያሉት የዓይን እማኞቹ፣ የ13 ዓመት ወጣትም ተደፍራለች ሲሉ ያዩትን ተናግረዋል፡፡

የታሳሪ ቤተሰቦች በበኩላቸው በሕወሓት ታጣቂዎች ‹‹የብልፅግና ደጋፊ ናችሁ›› ተብለው የታሰሩ ልጆቻቸው ከአንድ ዓመት በላይ እንደተፈረደባቸው፣ እስከ 150 ሺሕ ብር ድረስ ክፈሉ መባላቸውን በምሬት ተናግረዋል፡፡

ያለ ፍርድ የታሰሩና በታጣቂዎች ተገደው የተወሰዱ ወጣቶች ያሉበትን ሁኔታ አለማወቃቸው እንዳስጨነቃቸው የተናገሩት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፣ የሚመለከተው አካል መፍትሔ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል፡፡

Source: https://www.ethiopianreporter.com/

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *