News Sport

ኢትዮጵያዊቷ ትዕግስት አሰፋ የዓለም የማራቶን ክብረ ወሰንን ከሁለት ደቂቃ በላይ አሻሻለች

ትዕግሥት አሰፋ

የፎቶው ባለመብት,GETTY IMAGES

ዛሬ እሑድ መስከረም 13/2016 ዓ.ም በጀርመን በርሊን በተካሄደ 48ኛው የማራቶን ውድድር ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ትዕግሥት አሠፋ የዓለም የማራቶን ክብረ ወሰንን ከሁለት ደቂቃ በላይ በመስበር አሸነፈች።

የባለፈው ዓመት የበርሊን ማራቶን አሸናፊዋ ትዕግሥት፣ሁለት ሰዓት ከ11 ደቂቃ ከ53 ሰከንድ በመግባት ነው የዓለም የማራቶን ክብረ ወሰንን መያዝ የቻለችው።

የ29 ዓመቷ አትሌት እንደ አውሮፓውያኑ 2019 በተካሄደው የችካጎ ማራቶን በኬንያዊቷ አትሌት ብሪጊድ ኮስጌ ተመዝግቦ የነበረውን 2:14.04 ከሁለት ደቂቃ በላይ አሻሽላለች።

ትዕግሥት በባለፈው ዓመት የበርሊን ውድድር እንደ አውሮፓውያኑ በ2018 በኬንያዊቷ አትሌት ግላዲስ ቼሮኖ ተይዞ የነበረው 2:18:11 ሰዓት በማሻሻል የቦታውን ክብረ ወሰን ማስመዝገቧ ይታወሳል።

በዚህ ውድድር የትዕግሥት ድል ሦስተኛው ፈጣን የማራቶን ሰዓት ለመሆን በቅቶ ነበር።

በሌላ በኩል ዛሬ በተካሄደው የወንዶች ማራቶን የሁለት ጊዜ የኦሊምፒክ ቻምፒዮናው ኬንያዊው ኢሉድ ኪፕቼጌ ውድድሩን 2:02.42 በማጠናቀቅ ለአምስተኛ ጊዜ በማሸነፍ ታሪክ ሰርቷል።

በሴቶች ማራቶን ከትዕግሥት ሌላ፣ ዘይነባ ይመር፣ ሰንበሬ ተፈሪ፣ ደራ ዲዳ፣ ወርቅነሽ ኢዲሳ፣ እና ሔለን በቀለ ከአራተኛ እስከ ስምንተኛ ተከታትለው መግባት ችለዋል።

በወንዶች ደግሞ ታደሰ ተክሌ ሦስተኛ ሆኖ ሲያጠናቅቅ፣ ሀፍቱ ተክሉ እና አንዱዓለም በላይ አምስተኛ እና ስድስተኛ በመሆን አጠናቅቀዋል።

አትሌት ትዕግሥት ወደ ማራቶን ውድድር የገባችው ብዙም ትኩረት ሳይሰጣት ነው።

ከዚህ ውድድር በፊት በማራቶን የሩጫ ዘርፍ የተወዳደረችው ሁለት ጊዜ ብቻ ነበር።

ከባለፈው ዓመት የበርሊኑ ውድድር ቀድሞ የተሳተፈችው በሳዑዲ አረቢያ በተዘጋጀው የሪያድ ማራቶን ላይ ሲሆን 2:34:00 በሆነ ሰዓት ነበር ያጠናቀቀችው።

ዛሬ በበርሊን በተካሄደውና ሁለተኛዋ በሆነው የበርሊን ማራቶን ውድድር የራሷን ሰዓት በሦስት ደቂቃ ገደማ አሻሽላለች።

ለረዥም ጊዜያት የ800 ሜትር ሯጭ የነበረችው ትዕግሥት፣ በቅርቡ ነው ወደ ጎዳና ሩጫ ፊቷን ያዞረችው።

በ2016 ኦሊምፒክ ኢትዮጵያን ወክላ በ800 ሜትር ተሳትፋለች። ሆኖም ከግማሽ ፍጻሜው ማለፍ ባለመቻሏ ከውድድሩ ውጪ ሆና ነበር።

ትዕግሥት ከ800 ሜትር በተጨማሪ በ400 ሜትርም ስትወዳደር ቆይታለች።

አትሌቷ ቀደም ሲልም የግማሽ ማራቶን ውድድሮችን ለማሸነፍ በቅታለች።

በዓለም አትሌቲክስ ውድድር ውስጥ ከፍተኛ የሚባለው የፕላቲኒየም ደረጃ ያለው የበርሊን ማራቶን የተጀመረው እንደ አውሮፓውያኑ በ1974 ነው።

በጀርመን መዲና የሚካሄደው ውድድር ፈጣን ሰዓት ከሚመዘገብባቸው የማራቶን ውድድሮች መካከልም አንዱ ነው።

ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በዚህ ውድድር በተለያዩ ጊዜያት ያሸነፉ ሲሆን ኃይሌ ገብረ ሥላሴ እና ቀነኒሳ በቀለ ቀዳሚዎቹ ናቸው።

በሴቶች በኩል ጌጤ ዋሚ ውድድሩን ለማሸነፍ የቻለች የመጀመሪያዋ ኢትዮጵያዊት ናት።

ጌጤ እንደ አውሮፓውያኑ በ2006 እና በ2007 ውድድሩን በተከታታይ ማሸነፍ ችላለች።

ምንጭ፥ ቢቢሲ አማርኛ

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *