የኢትዮጵያውያን ማሕበር በሆላንድ
Press Release

ከኢትዮጵያውያን ማሕበር በሆላንድ ጊዜያዊ አመራር የተሰጠ መግለጫ

የኢካን ዓላማ በኔዘርላንድ የሚኖረውን ትውልደ ኢትዮጵያውያንን እና ኢትዮጵያውያንን ኮምዩኒቲይ የማሰባሰብ ሳይሆን የመከፋፋልና የማዳከም ተልኮን ያነገበ ነው።

አገር ! ለየአንድ ሠው ቋንቋው፣ ልማዱ፣ ባሕሉ፣ እምነቱ፣ አስተሳሰቡ፣ ወጉና በአጠቃላይ እሱነቱና ማንነቱ የሚከበርበት ብቸኛ ሥፍራ ነው።

ኢትዮጵያውያንም በስደት በሚኖሩባቸው አገራት ሁሉ እነኝህን በስደት ያጧቸውን የግልና የጋራ ማንነቶቻቸውን በአንድ ላይ ሆነው ለመዘከር እንዲያስችላቸው በማሰብ የተለያዩ ማዕከላትን በመፍጠር “ኢትዮጵያውያን በሚኖሩበት ስፍራ ሁሉ ኢትዮጵያም አለች” በሚያስብል ደረጃ ዓለምን በማስደመም እጅግ በጣም የሚደነቁና የሚታወቁ ናቸው።

በዚህ በኔዘርላንድ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንም ከ1982 ዓ ም ጀሞሮ “የኢትዮጵያውያን ማሕበር በሆላንድ (ኢማሆን)” ለሁሉም የአገራችንን ማህበረሰቦች ማዕከል የሆነ ሕዝባዊ ተቋም በሕጋዊነት በማቋቋም እስካሁን ድረስ በየጊዜው የሚገጥሙትን እንቅፋቶች ሁሉ በመቋቋም በነፃነት እየተቀሳቀሰ ያለ መሆኑ የሚታወቅ ነው።

የጋራ አገራችን ኢትዮጵያ በ1991 ዓ ም ቋንቋን መሠረት ያደረገ ከፋፋይና ዘረኛ ስርዓትን እንድትከተል ከተገደደችበት ዕለት ጀምሮ የኢትዮጵያውያን ማሕበር በሆላንድ (ኢማሆም) ልክ እንደ አገራችን ከባድ የህልውና ፈተና ተለይቶት ባያውቅም ከማንኛውም መንግስትና አፍራሽ ቡድን ፍላጎት እና ተጽኖን ተቋቁሞ የኖረና ወደፊትም ይህን ነፃነቱን ጠብቆ የኢትዮጵያውያን ማዕከል ሆኖ እንደሚቀጥል የሚታመን ነው።

በዚህ በምንኖርበት አገር ማንኛውም ሰው የሌላውን መብት አስካነካ ወይም እስካልተጋፋ ድረስ በፈለገው መልኩ የመደራጀት መብት እንዳለው የሚታወቅ ነው።
በኢትዮጵያዊነት ስምም በኔዘርላንድ መንግስት ዕውቅና የሚኖረው አንድ ህብረተሰብ (ኮምዩኒቲይ ) ብቻ እንደሆነ እየታወቀ “የጎባጣ አሽከር፡ እጎንብሶ ይሄዳል” እንዲሉ “እራሱን የኢትዮዽያውያን ኮሚኒቲ ማህበር በኔዘርላንድ (ኢካን)” በሚል ሕዝብን አደናጋሪ ስያሜ በመጠቀም ለፊታችን ጁን 15 ቀን 2024 ዓ ም ለሕዝብ ከአሠራጨው የጥሪ ደብዳቤ ለመረዳት ችለናል።

“ተደብቃ አርግዛለች፤ ሰው ሰብስባ ትወልዳለች” እንዲሉ ለመሆኑ እነዚህ ኃይሎች አዲስና ተመሳሳይ ማህበር የማቋቋም ደረጃ ላይ ከመድረሳቸው በፊት፦

1. ዛሬ ላይ ማህበር ወይም ሞት በማለት እየፈጉ ያሉት ስብስቦች (ወገኖቻችን) እነማን ናቸው? ይህስ በዚህ መልኩ የመሰባሰብ ብርቱ አቅምና ፍላጎትስ እስከዛሬ ለምን ተደብቆ ሊኖረ ቻለ? “ኢካን” የሚለው አህጽሮተ አጠራር ፍቺው ምንድን ነው?

2. እነኝህ ኃይሎች ቀድሞ በነበረው የኢትዮጵያውያን ማህበር በሆላንድ (ኢማሆ) ውስጥ አባል በመሆን ምን አይነት ተግባራዊ ተሳትፎ ነበራቸው? 99% ምንም።

3. ከዚህ በፊት የኢማሆ ዓላማና አሠራር ከእነሱ ፍላጎትና ዓላማ ጋር ተፃራሪ ወይም አብሮ የማይሄድ መሆኑን የሚያስረዳና ለግልጽ ሕዝባዊ ውይይት የሚጋብዝ እና ህብረተሰቡ እንዲተችበት በሰለጠነ መንገድ ለሕዝቡ ያጋሩት ወይም ህዝቡ በደፈናው እንዲያውቀው በይፋ የጋሩት (ያሰራጩት) ሰነድ ነበርን? ምንም

4. እስከ አፕሪል ወር 2023 ዓ ም ድረስ “ኢማሆን ለማጠናከር የተቋቋመ ጊዜያዊ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ” በሚል ማህበሩን ለመቆጣጠር በስውር ለተደራጀ ቡድን ለስድስት ወር ያህል ኢማሆን አስረክቡን ከንቱ ጥያቄያቸው፤ በወቅቱ እንደተቋም የኢማሆ ምላሽ የነበረው፤ በቅድሚያ በእነሱ በኩል የኢማሆ አባል ለመሆን የሚፈልጉትን የሰዎችን የስም ዝርዝር በሙሉ እንዲልኩለትና የእባልነት ቅጽ በመሙላት የኢማሆ አባል እንዲሆኑ በተደጋጋሚ በቃል እና በጽሑፍ ለቀረበላቸው ጥያቄ ለምን ተገቢውን ምላሽ መስጠት አልፈለጉም። ለምን? ወይም ከመጀመሪያው ጀምሮ የነዚህን የማህበር አፍቃሪ ማንነት ለኢማሆ ለማሳወቅ እስከ መጨረሻው ድረስ ለምን ፈሩ?

ሲጀመር በቀጥታ የኢማሆ አባል በመሆን ማህበሩን አንዳሉት ማጠናከር እየቻሉ፤ ለምን መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ ማቋቋም አስፈልጋቸው? ‘ሲያጋልጥ ይቆምጣል” ይላሉ ይህ ነው።

5. ለሕዝብ በተበተነው “በኢካን” የጥሪ ደብዳቤ መረሃ ግብር ላይ
“በኔዘርላንድ የሚገኙ የኢትዮጵያ ማህበራት አላማቸውን ያስተዋውቃሉ” ይላል። ለመሆኑ እነኚህ ማህበራት የተባሉትስ ለምን በስም አልተገለፁም? ምንስ አይነት ማህበራት ናቸው? ብዛታቸውስ ስንት ነው? በዚህ መሠረት ጥሪው ለኢማሆስ ለምን አልተላከለትም? ወይስ ኢማሆ የኢካንን መስፈርት አያሟላም ይሆን?

እነኝህን ከ1 እስከ 5 ለናሙና ያህል ያነሳናቸውን ቁልፍ የመፈተሻ ጥያቄዎች እያንዳንዱ በዚህ በኔዘርላንድ የሚኖረው የኢትዮጵያ ህብረተሰብ (ኮምዩንቲ) በባለቤትነት እና በኃላፊነት ስሜት እንዲጠይቅ እና ግፍን የማይፀየፉ ከፋፋዮችን ሁሉ አብዝቶ እንዲቃወም እና በሐቅ ለእውነት ዘብ እንዲቆም ከእደራ ጭምር ወገናዊ ጥሪያችንን እናቀርባለን።

እንደሚታወቀው ይህ በቋንቋና በነገድ (በጎሳ) አገራችንን የከፋፈለው ቆሻሻ ስርዓት ሲጀመር እንዱ መለያው በድርጅት ላይ ድርጅት መፈልፈል ነው። እኛም ኢትዮጵያውያን አብዛኞቻችን መፈክራችን ምን ይሁን ምን ብቻ እንኑርበት ስለሆነ እና ሲበዛ ደንታ ቢሶች ስለሆንን ለዚህ አይነት አታላይና አጭበርባሪ አሠራር እጅግ በጣም የተመቻቸን ነን።

በዘመነ ወያኔ ተቋቁመው የነበሩቱ “በኔዘርላንድ የኢትዮጵያ ህዳሴ ማህበርን” ጨምሮ በሙሉ ደብዛቸው ከስርዓቱ ጋር እንደጠፋ ሁሉ፤ ዛሬም ከዚህ ሊሞት እያጣጣረ ከአለ እጅግ ብልሹ የኦሮሙማ ስርዓት ጋር ታማኝነታቸውን ለመግለጽ የሚፈጉቱም በሙሉ ነገ ያለጥርጥር በተመሳስይ ሁኔታ እንደሚከስሙ የማይቀር ደረቅ ሐቅ ነው።

በመጨረሻም የኢካን እንቅስቃሴ በኢትዮዽያ ስልጣኑን በተቆጣጠረው አካል ወኪሎች ስር የስርዓቱን ገበና እና እውነተኛ ገፁን በመሸፋፈን ተልእኮ ላይ መሰማራቱን ለብዙሃኑ አገር ወዳድና ስለሰብአዊ መብት የሚቆሙና የሚቆራቆሩ ሁሉ እንዲያውቁት በማለት ይህንን የተቃውሞ መግለጫ ለማውጣት ተገደናል።

በአሁኑ ወቅት በአገራችንና በሕዝቧ ላይ የሚፈፀመውን ግፍ በውጭ ታዛቢዎች ሳይቀር በሰፊው እየተዘገበ ነው።

ባለፈው ወር የኔዘርላንድ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ለፓርላማው ማብራሪያ በመስጠት በኢትዮዽያ ስደተኞች ላይ የአቋም ለውጥ እንዲደረግ መገደዱን ይፋ አድርጏል። ዘገባውን ለማንበብ ይህን ከታች ያለውን ማስፈንጠሪያ ይጠቀሙ።

https://www.rijksoverheid.nl/documenten/kamerstukken/2024/05/29/tk-landenbeleid-ethiopie

በአገራችን ያለው እውነታ ይህ ሆኖ ሳለ ምንም ችግር እንደሌለ በሚመስል መልኩ እና በውጭ የሚኖረውን ኢትዮዽያዊ ህብረተሳብ በመከፋፈልና በአገር ቤት የቁም ፍዳውን እያየ ላለው ወገኑ ድምፁን የሚያሰማባቸውን ተቋማቱን የማዳከም ተልኮን አጥብቀን እየኮነንን። በኢማሆም ላይ እየተደረገ ያለውን ተመሳሳይ የመከፋፈልና የማዳከም እንቅስቃሴን አጥብቀን እዬተቃወምን፤ ሌላውም አገር ወዳድ እና ግፍን የሚፀየፍ ሁሉ አብሮን እንዲቆም ጥሪ እናደርጋለን።

ኢማሆ ግፍን የማይፀየፉ ከፋፋዮችን አብዝቶ ይቃወማል!!!

የኢትዮጵያውያን ማሕበር በሆላንድ ጊዜያዊ አመራር

ሰኔ 11 ቀን 2024 ዓ ም

Email: info.venholland@gmail.com, WhatsApp:+31617547320, KvK Nummer: 55481345

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *